Abstract:
ይኽ ጥናት “ንጽጽራዊ የዘር አወጣጥ ጥናት በዋድላ፣ በዋሸራ እና በጎንጅ የቅኔ አብያተ ጉባኤያት” በሚል ርእስ ላይ ተመሥርቶ የተሠራ ሲኾን፣ ዋና ዓላማዉም በሦስቱ አብያተ ጉባኤያት መካከል የዘር አወጣጥ ልዩነት መኖር እና አለመኖሩን መመርመር ነው፡፡ አጥኚዉን ለዘህ ጥናት እና ምርምር ሥራ ያነሣሣዉ ዐቢይ ምክንያት በሦስቱ የቅኔ አብያተ ጉባኤያት ውስጥ ተምረው በወጡ ምሁራን የተጻፈ የግእዝ መዙግበተ ቃላት፣ የሰዋስው መጻሕፌት እና ከሦስቱ አብያተ ጉባኤያት ውጭ በኾኑ ምሁራን የተጻፈ መጻሕፌት የዘር አወጣጥ ልዩነት በማሳየታቸው ነው፡፡ ይኽ ጥናትም ከግብ ይደርስ ዘንድ ዐይነታዊ የምርምር ዘዴን በመጠቀም ጠቃሚ መረጃዎች በሰነድ ፍተሻ እና በቃለ መጠይቅ ከተሰበሰቡ በኋላ ዐላማ ተኮር ንሞናን በመጠቀም መረጃዎቹ በገላጪ ንጽጽራዊ የመረጃ መተንተኛ ተተንትነው ቀርበዋል፡፡ ለጥናት በተመረጡ መጻሕፍት ውስጥ ዘሮች ከሥርወ ቃላት ላይ ሲመሠረቱ የአሥራወ ቃላቱ መነሻ፣ ኹለት ተከታታይ መነሻ፣ መድረሻ፣ እንዲኹም መነሻ እና መድረሻ ፊደላት ከዘሮች ላይ ተጎረደው ታይተዋል፡፡ እንዲኹም በዘር መካከል ባዕድ ፊደሌልበመጨመር የተመሠረተ ዘር፣ የደጊመ ፊደል ቅርጽ ከሌለው ሥርወ ቃል ባለ ደጊመ ፊደል ዘር የተመሠረተ ዘር እና ድርብ ምእላዳትን ይዞ የተመሠረተ ዘር መኾኑን ማረጋገጥ ተችሏል፡፡ በጥናቱም በትርጉም እና በፊደል የማይገናኝ የዘር አወጣጥ፣ ከፊል ፊደላዊ እና ምስጢራዊ የዘር አወጣጥ፣ ሙለ ምስጢራዊ የዘር አወጣጥ፣ በዘር መካከል ባእድ ፊደል በመጨመር የተመሠረተ ዘር፣ ከነጠላ ሥርወ ቃል በደጊመ ፊደል የተመሠረተ ዘር እንዲኹም ድርብ ምእላዳትን በመያዝ የወጣ ዘር የሚሉት ርእሰ ጉዳዮች በተገቢው መንገድ ተተንትነው ቀርበዋል፡፡ በጥናታዊ ግኝቱም በሦስቱ የቅኔ አብያተ ጉባኤያት መካከል እና እንዲኹም በሌሎች ምሁራን ዘንድ የዘር አወጣጥ ልዩነት እንዳለ ተረጋግጧል፡፡ በመጨረሻም በሥርወ ቃል የሚጀምር፣ የተውሶ ቃላትን፣ ነባር ቃላትን እና ዘርን ለይቶ የሚያቀርብ የግእዝ መዛገበ ቃላት የዘመናዊ እና የአብነት የትምህርት ተቋማትን ማእከል አድርጎ ቢዘጋጅ እና ተደራሽ የሚኾንበት መንገድ ቢመቻች፤ ማንኛዉም የዘር ዐይነት ከሥርወ ቃል ሲወጣ በፅንሰ ሐሳብ ሳይኾን፣ ትርጉምን እና መልክአ ፊደልን ብቻ መሠረት ያደረገ ቢኾን፣ ግላዊ የኾነ የዘር አወጣጥን ለመቀነስ ሲባል፣ የግእዝ መዛግብተ ቃላት ሲዘጋጁ የአርትዖት ሥራ የሚሠራ ተቋም ቢቋቋም፣ በግእዝ ቋንቋ ዙሪያ የተሠሩ ጥናቶች እና ግኝቶቻቸው ለሚመለከታቸው ግለሰቦች እና ተቋማት እንዲደርሱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኀላፊነታቸውን ቢወጡ መልካም መኾኑን የሚጠቁሞ ሐሳቦች ተካተው ቀርበዋሌ፡፡