Abstract:
የዚህ ጥናት ዋና ዓላማ የጥያቄ-መልስ ትስስር ብልኃት አንብቦ በመረዳትና በጥልቀት
በማሰብ ችሎታ፣ እንዲሁም በማንበብ ግለብቃት እምነት ላይ ያለውን ተጽእኖ መመርመር
ሲሆን ፍትነትመሰል ቅድመና ድኅረትምህርት ፈተና ባለቊጥጥር ቡድን ንድፍን ተከትሎ
ተከናውኗል። በ2016 ዓ.ም. በባሕር ዳር ከተማ በአዲስ አምባ የመጀመሪያ ደረጃ
ትምህርትቤት ከስድስት የሰባተኛ ክፍል መማሪያ ክፍሎች መካከል ዐራቱ በእጣ ተመርጠው
በክፍሎቹ ይማሩ የነበሩ 222 ተማሪዎች በጥናቱ ተሳትፈዋል። የፍትነት ቡድኑ ተማሪዎች
በጥያቄ-መልስ ትስስር ብልኃት፣ የቊጥጥር ቡድኑ ደግሞ በሥርዓተትምህርቱ በተመላከቱ
ብልኃቶች ለ14 ክፍለጊዜ አንብቦ መረዳት ተምረዋል። ቅድመና ድኅረትምህርት መረጃዎች
አንብቦ በመረዳትና በጥልቀት በማሰብ ፈተናዎች፣ እንዲሁም በማንበብ ግለብቃት እምነት
መጠይቅ ተሰብስበዋል፡፡ በቅድመትምህርት መረጃዎች የፍትነቱና የቊጥጥር ቡድኑ
ተማሪዎች የጾታና የዕድሜ ተመጣጣኝነት በካይ ካሬ ቴስት፣ የዳራዊ ዕውቀት አቻነት
ደግሞ በባለብዙ ተላውጦ ልይይት ትንተና ስልት ተፈትሾ የቡድኖቹ አቻነት (p>.05)
ተረጋግጧል፡፡ ድኅረትምህርት መረጃዎች የተተነተኑት በመዋቅራዊ ስሌት ሞዴል ነው።
የትንተናው ውጤት እንዳመላከተውም የጥያቄ-መልስ ትስስር ብልኃት በተማሪዎች አንብቦ
የመረዳት ችሎታ (β= .310, t= 4.277, p<.001)፣ በጥልቀት በማሰብ ችሎታ (β= .438, t=
5.873, P<.001) እና የማንበብ ግለብቃት እምነት (β= .549, t= 5.092, p<.001) ላይ ቀጥተኛ
አወንታዊ ተጽእኖ አለው። በተጨማሪም ብልኃቱ በጥልቀት የማሰብ ችሎታን በማሳደግ (B=
.807, t= 2.831, P<.01) እና የማንበብ ግለብቃት እምነትን በማጎልበት (B= 1.386, t= 3.013,
p<.01)፣ አንብቦ በመረዳት ችሎታ ላይ ኢቀጥተኛ አወንታዊ ተጽእኖ እንዳለው የተገኘው
መረጃ አረጋግጧል። በጥልቀት የማሰብ ችሎታንና የማንበብ ግለብቃት እምነትን በጥምረት
በማሻሻል አንብቦ በመረዳት ችሎታ ላይ ያሳደረው ተጽእኖ ግን አወንታዊ አይደለም (B=
.096, t= 1.021, p=.129)፡፡ በዚህም (ከተጣማሪ ተላውጦዎች የአዋዳጅነት ሚና በስተቀር)
በዐማርኛ ቋንቋ ማንበብን በጥያቄ-መልስ ትስስር ብልኃት ማስተማር፣ የተማሪዎችን አንብቦ
የመረዳት ችሎታ ለማሻሻል ቀጥተኛና ኢቀጥተኛ አወንታዊ ተጽእኖ እንዳለው ተረጋግጧል።
ከተገኘው ውጤት በመነሳትም ሥነትምህርታዊና ምርምራዊ ምክረሐሳቦች ተመላክተዋል፡፡
ቊልፍ ቃላት፤ የጥያቄ-መልስ ትስስር ብልኃት፣ አንብቦ መረዳት፣ በጥልቀት ማሰብ፣
የማንበብ ግለብቃት እምነት