Abstract:
የዚህ ጥናት ዋና ዓላማ ልዕለአእምሯዊ የመጻፍ ብልኃቶች በተማሪዎች የመጻፍ ችሎታ፣
በብልኃቶቹ ግንዛቤና በመጻፍ ግለብቃት እምነት ላይ ያላቸውን ቀጥተኛና ኢቀጥተኛ ተጽዕኖ
መፈተሽ ነበር፡፡ ጥናቱ ፍትነትመሰል የምርምር ስልትን በመከተል በሰለሞን ባለአራት ቡድን
ንድፍ ተካሂዷል፡፡ ጥናቱ የተካሄደው በደሴ ከተማ በመምህር አካለወልድ ኹለተኛ ደረጃ
ትምህርትቤት ሲኾን የጥናቱ ተሳታፊዎችም በ2016 ዓ.ም. በዚሁ ትምህርትቤት ይማሩ ከነበሩ
15 የዘጠነኛ ክፍል መማሪያ ክፍሎች መካከል በአንድ መምህር ከሚማሩ 9 ክፍሎች በቀላል የእጣ
ንሞና በተመረጡ አራት የመማሪያ ክፍሎች የሚማሩ 155 ተማሪዎች ነበሩ፡፡ የፍትነት ቡድኑ
ተማሪዎች የመጻፍ ትምህርቱን በልዕለአእምሯዊ የመጻፍ ብልኃቶች፣ የቍጥጥር ቡድኑ
ተማሪዎች ደግሞ በክፍል ደረጃው መደበኛ ሥርዐተትምህርት መሠረት ለ10 ሳምንታት
ተምረዋል፡፡ ከምርምሩ በፊት ኹለቱ ቡድኖች፣ ከምርምሩ በኋላ ደግሞ አራቱም ቡድኖች
ተመሳሳይ ቅድመትምህርትና ድኅረትምህርት የመጻፍ ፈተና ተፈትነዋል፤ ልዕለአእምሯዊ የመጻፍ
ብልኃቶች ግንዛቤና የመጻፍ ግለብቃት እምነት የጽሑፍ መጠይቆችም ሞልተዋል፡፡
በቅድመትምህርት መረጃዎች የጥናቱ ተሳታፊዎች የፆታ ስብጥር በካይ ካሬ ቴስት፣ የዕድሜ
ተመጣጣኝነት በነጻ ናሙና ቲ-ቴስት እንዲሁም የዳራዊ ዕውቀት አቻነት በባለብዙ ተላውጦ
ልይይት ትንተና ዘዴ ተፈትል፡፡ በተጨማሪም የቅድመትምህርት ልኬታው ተናጥላዊና
መስተጋብራዊ ተጽዕኖ በድኅረትምህርት ውጤቶቹ ላይ ሊፈጥረው የሚችለው ልዩነት በመንታ
መንገድ ባለብዙ ተላውጦ ልይይት ትንተና ዘዴ ተፈትሿል። ድኅረትምህርት መረጃዎችም
በመዋቅራዊ እኩልዮሽ ሞዴል ዘዴ ተተንትነዋል፡፡ የድኅረትምህርት የትንተና ውጤቱ
እንዳመለከተው መጻፍን በልዕለአእምሯዊ የመጻፍ ብልኃቶች መማር በተማሪዎች የመጻፍ ችሎታ
(β = .409, t = 3.754, p < .001)፣ በልዕለአእምሯዊ የመጻፍ ብልኃቶች ግንዛቤና (β = .743, t = 5.752,
p< .001) በመጻፍ ግለብቃት እምነት (β = .784, t = 7.459, p = <.001) ላይ ቀጥተኛ አስተዋፆ
አላቸው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ልዕለአእምሯዊ የመጻፍ ብልኃቶች በልዕለአእምሯዊ የመጻፍ ብልኃቶች
ግንዛቤ አማካይነት (B = 4.892, t = 2.484, p = .018) እንዲሁም በመጻፍ ግለብቃት እምነት
አማካይነት (B = 5.741, t = 2.092, p = .013) የመጻፍ ችሎታን የማሻሻል ኢቀጥተኛ ሚና አላቸው፡፡
በመኾኑም መጻፍን በልዕለአእምሯዊ የመጻፍ ብልኃቶች ማስተማር የተማሪዎችን የመጻፍ
ችሎታ፣ የብልኃቶቹን ግንዛቤና የመጻፍ ግለብቃት እምነትን በማጎልበት ረገድ ቀጥተኛ አስተዋፆ
እንዲሁም በብልኃቶቹ ግንዛቤና በመጻፍ ግለብቃት እምነት አማካይነት በኩል በመጻፍ ችሎታ ላይ
ኢቀጥተኛ አስተዋፆ አላቸው፤ ወደሚል መደምደሚያ ተደርሷል፡፡ ከጥናቱ ውጤት በመነሳትም
ሥነትምህርታዊ ምክረሐሳቦችና የወደፊት የምርምር አቅጣጫዎች ተጠቁመዋል