Abstract:
አህፅሮተጥናት
የዚህ ጥናት አቢይ አላማ የተማሪዎችን የማንበብ ተነሳሶት፣ የማንበብ መጠንና አንብቦ የመረዳት ችሎታ ተዛምዶ መፈተሽ ነው፡፡ የጥናቱ ተሳታፊዎች በባህርዳር ከተማ በግንቦት ሃያ ክፍለ ከተማ በዶናበርበር አንደኛ ደረጃ ትምህርትቤት በ2010 ዓ.ም ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ከሚገኙ 369 ተማሪዎች መካከል በእድል ሰጪ ንሞና ዘዴ የተመረጡ 56 የ7ኛ ክፍል ተማሪዎች ናቸው፡፡ ጥናቱ ተዛምዷዊ በመሆኑ የተማሪዎቹን አንብቦ የመረዳት ችሎታ ለማወቅ ፈተና እንዲፈተኑ፣ የማንበብ ተነሳሶትና የማንበብ መጠንአቸውን ለማወቅ ደግሞ የፅሁፍ መጠይቅ እንዲሞሉ ተደርጓል፡፡ በነዚህም መረጃዎች ተሰብስበዋል፡፡ የተሰበሰቡት መረጃዎችም በፒርሰን የተዛምዶ መወሰኛ ቀመር ተተንትነዋል፡፡ ውጤቱ እንደሚያሳየው በተማሪዎች የማንበብ ተነሳሶትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ መካከል ጉልህ አዎንታዊ ተዛምዶ ታይቷል (r=0.484, P<0.05)፡፡ በተመሳሳይ በተማሪዎች የማንበብ መጠንና አንብቦ የመረዳት ችሎታ መካከል ጉልህ አወንታዊ ተዛምዶ ታይቷል (r=0.396, P<0.05)፡፡ በተጨማሪም በድህረት መጣኝ ትንተና ስሌት መሰረት የተማሪዎች የማንበብ ተነሳሶትና የማንበብ መጠን በተማሪዎች አንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ ያለው ድርሻ በስታስቲክስ ጉልህ ሆኖ ተገኝቷል (R2= 0.308, F=11.559,P<0.001)፡፡ ነገርግን የማንበብ ተነሳሶት ከማንበብ መጠን በተሻለ ሁኔታ አንብቦ የመረዳት ችሎታን የመተንበይ ድርሻው ከፍተኛ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ በዚህም መሠረት የማንበብ ተነሳሶት የአንብቦ መረዳት ችሎታን የመተንበይ ተፅዕኖ (B=.405 የቲ ዋጋ 3.366 የስሕተት ይሆንታ መጠን 0.001) ሆኖ ተገኝቷል፡፡ በተመሣሣይም የማንበብ መጠን የአንብቦ መረዳት ችሎታን የመተንበይ ተፅዕኖ (B=.285, ቲ 2.346, P< 0.023) ሆኗል፡፡ በጥናቱ ውጤት መሰረትም የተማሪዎችን የማንበብ ተነሳሶትና የማንበብ መጠን የሚያጎለብቱ ስልቶችን ከአንብቦ መረዳት ችሎታ ጋር በማዛመድ በመማርማስተማር ሂደት ትኩረት ሰጥቶ መጠቀም ጠቃሚ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡