Abstract:
ይህ ጥናት በፍስሃ ማንጠግቦት ሰው እኮ!? (2002 ዓ.ም.) ረጅም ልቦለድ ውስጥ የተመረጡ
ጭብጦች በዳያስፖራው ኑሮ ላይ እንዴት እንደተንፀባረቁ ማሳየት ላይ ትኩረቱን አድርጓል፡፡
በጥናቱ ሂደት የሚመለሱ እና የዳያስፖራውን ኑሮ ሊያሳዩ የሚችሉ ሦስት የጥናቱ ጥያቄዎች
ተቀርፀዋል፡፡ የዳያስፖራ ኑሮን ከድኅረ-ቅኝ ግዛት ሂስ አንፃር መፈናቀል፣አገርን መናፈቅ፣
ትውስታና መርሳት እና ማንነትን መፈለግ በሚሉት ጭብጦች ላይ በማተኮር ትንተና
ተካሂዷል፡፡ ጥናቱ አይነታዊ የምርምር ዘዴን የተከተለ ሲሆን የጭብጥ ትንተና ሥልትን
በመጠቀም ልቦለዱን ከንድፈ-ሃሳቡ ጋር በማዛመድ ገፀ-ባህሪያት ኑሯቸውን ለማሸነፍ
የሚያደርጉት ጥረት ከተመረጡት አራቱ ጭብጦች አንፃር ተንትኗል፡፡ እነዚህ ጭብጦች
ከዳያስፖራው ኑሮ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዳላቸው በትንተና ክፍሉ ተመላክቷል፡፡
ከትንታኔውም መፈናቀል፣አገርን መናፈቅ፣የባዕድ ኑሮ ከጠበቁት በተቃራኒው መሆን፣
ባይተዋርነት፣ተስፋ መቁረጥ፣ብቸኝነት፣ ክህደት፣ለመኖር ሲሉ ሥራ ሳያማርጡ መሥራት፣
የአዕምሮ ሕመም፣ከሥራ መፈናቀል፣የባህል ግጭት፣ሞት፣ፍቺ፣ ማጣት፣ዘርን አለመተካት፣
በኑሮ ደስተኛ አለመሆን፣የልጆች መበተን እና ሱስ፣በወንዶች ዘንድ የፆታዊ ግንኙነት ችግር እና
ሌሎችም በገፀ-ባህሪያት ዘንድ እንደተስተዋሉ ጥናቱ አመላክቷል፡፡ በመሆኑም በልቦለዱ ውስጥ
የተቀረፁ ዳያስፖራ ገፀ-ባህርያቶች ኑሮ በችግር እና በውጣ ውረድ የተሞላ እና የተመሰቃቀለ
ነው ብሎ ማጠቃለል ይቻላል፡፡