Abstract:
አህፅሮተጥናት
የዚህ ጥናት ዋና ዓላማ በተማሪዎች ድርሰት የመፃፍ ተነሳሽነትና ድርሰት የመፃፍ ችሎታ መካከል ያለውን ተዛምዶ መመርመር ነው፡፡ በመሆኑም ጥናቱ ተዛምዷዊ ስልትን ተከትሏል፡፡ የጥናቱ ተሳታፊዎችም በባህርዳር ከተማ ሹምአቦ አጠቃላይ 2ኛ ደረጃና መሰናዶ ትምህርትቤት በ2011ዓ.ም በ9ኛ ክፍል ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ከሚገኙ ተማሪዎች ውስጥ በቀላል የዕጣ ናሙና ዘዴ የተመረጡ 101 ተማሪዎች ናቸው፡፡ የጥናቱን ኣላማ ከግብ ለማድረስም የሚያስፈልጉ መረጃዎች በፅሁፍ መጠይቅና በፈተና ተሰብሰበዋል፡፡ መረጃዎቹ በገላጭና ተንባይ ስታትስቲክሶች አማካይነት ተተንትነው ተብራርተዋል፡፡ በመረጃ ትንተናው መሰረት ጥናቱ የተማሪዎች ድርሰት የመፃፍ ተነሳሽነት እንዳላቸው አሳይቷል፡፡ የተማሪዎች ድርሰት የመፃፍ ችሎታ ከአማካይ በላይ ሆኖ ታይቷል፡፡ በተጨማሪም በተማሪዎች ድርሰት የመፃፍ ተነሳሽነትና ድርሰት በመፃፍ ችሎታ መካከል አዎንታዊ ተዛምዶ (r=.503, p<.05) እንዳለ ጥናቱ አሳይቷል፡፡ ከዚህም ሌላ ተነሳሽነት ድርሰት የመፃፍ ችሎታ የመተንበይ ድርሻው ከፍተኛ መሆኑን (R² = .254፣ F= .33.62 ፣ P<.05) የጥናቱ ውጤት አመልክቷል፡፡ በጥናቱ መሰረት አማርኛ የሚያስተምሩ መምህራን የተማሪዎች ድርሰት የመፃፍ ተነሳሽነት ድርሰት በመፃፍ ችሎታ ላይ የራሱ የሆነ ድርሻ እንዳለው በመገንዘብ ትምህርቱን የተማሪዎችን ስሜት በሚያነሳሳ መልኩ ቢያቀርቡ፣ እንዲሁም የተማሪዎችን ድርሰት የመፃፍ ተነሳሽነት ለማጠናከር የሚረዱ ተግባራትን ቢያከናውኑ፣ የስርዓተትምህርት ቀራጮች መርሀትምህርት ሲነድፉ፣ የትምህርት መሳሪያዎች አዘጋጆች የትምህርት መሳሪያዎችን ሲያዘጋጁ፣ የተማሪዎችን ድርሰት የመፃፍ ተነሳሽነትን ላይ ትኩረት መስጠት ቢችሉ፣ በዘርፉ ጥናት ለማካሄድ የሚሹ ተመራማሪዎች ሰፋ ያለ ሙከራዊ ጥናት ቢያካሂዱ የተማሪዎችን ድርሰት የመፃፍ ችሎታ ለማዳበር የሚያደርገው አስተዋጾ ቀላል አይሆንም፡፡